ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ

ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ በወሎ ክፍለ ሀገር በአሁኑ አጠራር በአማራ ክልል ደቡብ ወሎ ዞን በመቅደላ ወረዳ በቅን አምባ መድኃኔዓለም አጥቢያ ሚያዝያ 23-1932 ዓ.ም ተወለዱ፡፡

እድሜያአቸው ለትምህርት እንደደረሰ በዳውንት ወረዳ የቀይ ቅድስት ማርያም ቤተ ቤተ-ክርስቲያን ከፊደል እስከ ግብረ ሰሞን በመቀጠልም ውዳሴ ማርያም ዜማን፣ መስተገብዕ፣ አርባዕትና ክስተት አርአያም ሠለስት ተምረዋል፡፡

በተጫማሪም ቅኔን ከመሪጌታ ታደሰ ለመጀመሪያ ጊዜ በመማር በመቀጠልም የቅኔውን ሙያ በበለጠ ለማሻሻል በደላንታ ባባ ነአኩተለአብ ከተባለው ቦታ ቅኔን ለሁለተኛ ጊዜ ከነአገባቡ ጠንቅቀው ተምረዋል፡፡
ብፁዕነታቸው ዜማን በብልባላ ጊርጊስ፣ ዜማን፣ ዝማሬ መዋስዕት ፣ ጾመ ድጓንና ምዕራፍን በጎንደር ቅድስት ማርያም በሚገባ አጠናቀው ተምረዋል፡፡ በተጨማሪም በጎንደር ተንሶየ ቅድስት ማርያም እና በወገራ ቅድስት ማርያም ቤተ-ክርስቲያን ከ4 ዓመታት በላይ አቋቋምን ተምረው አስመስክረው በመምህርነት ተመርቀው ወጥተዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ በ1966 ዓ.ም ወደ አዲስ አበባ በመሄድ አዲስ አበባ መንበረ መንግስት ቅዱስ ገብርኤል የሐዲሳት ትርጓሜ ትምህርት እና በደብረሊባኖስ የዳዊትን ትርጓሜ ጠንቅቀው ተምረዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ በመማር እንዲሁም በማስተማር በርካታ ዓመታትን በወላይታ እና በዙሪያዉ በሚገኙ ወረዳዎች በመዘዋወር ስብከተ ወንጌልን በማስፋፋት፣ ሰንበት ት/ቤት በማደራጀት በስነ ጥበበ ትምህርት ያስተምሩ ነበር፡፡ በክረምት ወቅትም ለወጣቶች ኮርስ በመስጠት በርካታ ሰባኪያነ ወንጌል አፍርተዋል።

ድቁናን ከብፁዕ አቡነ ገብርኤል ምንኩስና ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቅስና ከብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ የሲዳሞ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተቀብለዋል። በኋላም ቁምስናን ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ተቀብለዋል።

ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ከ1968 ዓ.ም ጀምሮ እስከ 1971 ድረስ በመንበረ ፓትርያርክ ጠ/ቤተ ክህነት በልዩ ጽ/ቤት፣ በሰበካ ጉባኤና በስብከተ ወንጌል መመሪያዎች አገልግለዋል፡፡

ከ1971 እስከ 1972 ዓ.ም የምስካየ ኅዙናን መድኃኔዓለም አንድነት ገዳምን በሰላምና በፍቅር እየመሩ ቆይተዋል፡፡

ብፁዕነታቸዉ የጵጵስና ሹመት እስከሚሰጥበት ጊዜ ድረስ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናቸዉን በተለያዩ ሀገራት በተለያየ የሥራ ደረጃ አገልግለዋል፡፡

ከህፃንነታቸው ጀምሮ በትምህርት ቤት በኋላም ከደብረ ሊባኖስ እስከወላይታ ከሲዳሞ እስከ ሸዋ በሥራ አስኪያጅነትና በሰበካ ጉባኤ አመራርነት፣ በስብከተ ወንጌል ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ በምስካየ ኅዙናንና ህፃናት ማሳደጊያ መምሪያ በተለያዩ የሥራ ኃላፊነቶች የሰጧቸውን አገልግሎቶች መነሻ በማድረግ ግንቦት 30 ቀን 1979 ዓ.ም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ተብለው ሢመተ ጵጵስና ተቀብለዋል። ከህዳር ወር 1980 ዓ.ም ጀምሮ የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመሆን እያገለገሉ ይገኛሉ።
በሰሜን ወሎና ዋግኸምራ እስከገጠር በመዘዋወር በርካታ መንፈሳዊ፣ ሰብዓዊና ቁሳዊ ልማት አስፋፍተዋል።