ምግባረ ሠናይ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ችግረኞችን ለመርዳት ምግባረ ሠናይ (የበጎ አድራጎት) ክፍል ከጠቅላይ ቤተ ክህነት እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት በማቋቋም በሰፊው ትሠራለች።

ምግባረ ሠናይ ምእመናንን፣ በጎ አድራጊ ግለሰቦችንና ድርጅቶችን በማስተባበር ችግረኞች፣ ጧሪና ረዳት የሌላቸው ሽማግሌዎችና ባልቴቶች በቤተ ክርስቲያን አካባቢ መጠለያና ምግብ እንዲያገኙ ማመቻቸት፤ ጤናቸውንም በመንከባከብ ችግረኞች መንፈሳዊና ሥጋዊ አኗኗራቸው የተሻለ እንዲሆን ክትትልና ድጋፍ በማድረግ የስነ ልቦና ጥገና የሚደረግበት ዘርፍ ነው። ወላጅ ወይም አሳዳጊ የሌላቸው ሕፃናት ጊዜያዊና ዘላቂ ርዳታ የሚያገኙበትን መንገድም ያመቻቻል።

ሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ወላጆቻቸውን በተለያየ ምክንያት አጥተው አሳዳጊ የሌላቸው ሕፃናትን ከተለያዩ ረጅ ድርጅቶች ጋር በመተባበር አሳድጎ ለቁም ነገር በማብቃት የእረዥም ጊዜ ልምድ አለው። ሀገረ ስብከቱ ገነት የሕፃናት መርጃ ማዕከልን በማቋቋም በርካታ ለችግር ተጋላጭ ሕፃናትን መታደግ ችሏል።

ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ (የክብር ዶ/ር) ከ2013 ዓ.ም ጀምሮ በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል በተከሰተው የሰላም እጦት (ጦርነት) ምክንያት ወላጆቻቸውን ያጡ ሕፃናትን በቋሚነት ለመንከባከብና ለማሳደግ በውጭ ሀገር ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን የገንዘብ ድጋፍ አግኝተዋል።

በማዕከሉ 20 ሕፃናትን ለመቀበል ቅድመ ዝግጅት እየተደረገ ነው። በገነት ሕፃናት መርጃ ማዕከል ውስጥ እንክብካቤ ከሚደረግላቸው በተጨማሪ 10 ሕፃናት ከአሳዳጊዎቻቸው ጋር ሆነው እንዲያድጉ ወጭአቸው ይሸፈንላቸዋል።

ሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት በብፁዕ አቡነ ኤርምያስ አስተባባሪነት ከበጎ አድራጊዎች በተገኘ ከ1 ሚሊዮን 420 ሽህ ብር በላይ ገንዘብ በጦርነቱ ምክንያት ቤትና ንብረታቸው የወደመባቸው በተለይም የእርሻ በሬዎቻቸው የታረዱባቸው አርሶ አደሮች እስካሁን ከ60 በላይ ለሚሆኑት አንዳንድ በሬና የዘር መግዣ ጥሬ ገንዘብ ተለግሷል።

የሃይማኖት ልዩነት ሳይደረግ የእለት ደራሽ ምግብ፣ ጥሬ ገንዘብና ቁሳቁስ ለበርካታ ችግረኞች ድጋፍ የተደረገ ሲሆን በጦርነቱ የወደሙ ሁለት የጤና ተቋማትን መልሶ በማቋቋም የሕክምና ቁሳቁስና መድኃኒት ድጋፍ ተደርጓል።

ከሀገረ ስብከቱ በተጨማሪ የደብረ ሮሐ ቅዱስ ላሊበላ አረጋዉያን መንከባከቢያ ማዕከል በርካታ ጧሪ የሌላቸውን ተቀብሎ እየተንከባከበ ይገኛል።